October 5, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

የጎንጋ ህዝቦች የልማት፥ የወንድማማችነትና የአብሮነት ፎረም እየተካሄደ ነው።

የአንድ ህዝብነት ታሪካቸውን ከዘመናት በኋላ ያደሱት የጎንጋ ህዝቦች ማለትም ካፋ፥ሸካ እና የቦሮ ሺናሻ ህዝቦች አንድነታቸውን ለማጠንከርና በርካታ የጋራ እሴቶቻቸውን ለማስተዋወቅ በሸካ ዞኗ ዋና ከተማ ቴፒ ተገናኝተዋል።ፎረሙን በይፋ የከፈቱት የደቡብ ምእራብ ህዝቦች ምክትል ርእሰ መስተዳድርና የክልሉ ግብርና ቢሮ ሀላፊ እንዲሁም የክልሉ ርእሰ መስተዳድር ተወካይ አቶ ማስረሻ በላቸው የጎንጋ ህዝቦች በኢትዮጰያ ታሪክ ውስጥ ትልቅ ቦታ የነበራቸው መሆኑን ተናገረው ከ15ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ በተለያዩ ፖለቲካዊና ማህበራዊ ምክንያቶች ተራርቀው መቆየታቸውን አውስተው አሁን በተፈጠረው መልካም አጋጣሚ ሦስቱ ህዝቦች የጋራ የአንድነት ፎረማቸውን ለስድስተኛ ጊዜ ማድረጋቸውን ተናግረዋል። የሸካ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አበበ ማሞ የቦሮ ሺናሻ፥ የካፋ እና የሸካ ወንድምና እህት ህዝቦች በቋንቋ በባህልና በአኗኗር ዘዬ የተቀራረቡ ህዝቦች ከመሆናቸው ጋር ተያይዞ የአንድነት ፎረም መጀመራቸው የኋላ ታሪካቸውን ለማጥናት ያለው ፋይዳ የጎላ በመሆኑ የዞኑ መንግስትም ሆነ የዞኑ ህዝብ ድጋፉን አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።የጎንጋ ህዝቦች የህዝብ ለህዝብ ልማትና ትብብር ሰብሳቢ አቶ ክፍሌ ገብረማርያም በበኩላቸው ሦስቱ ህዝቦች ምንም እንኳን በተለያየ ጂኦግራፊያዊ መገኛ የሚኖሩ ቢሆንም ህገ መንግሥት በሰጣቸው ምቹ ሁኔታ ባህልና ታሪካቸውን እርስ በርስ የሚማማሩበት መድረክ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረው ቀጣይም ህጋዊ እውቅና ባለው አካል ፍሬያማ ተግባር እንደሚከናወን ገልጸዋል።

ዘጋቢ አስታውሰኝ በቃሉ