October 4, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

እስራኤል በሊባኖስ የከፈተችው ውግያ የጋዛውን ጦርነት ያህል ይከፋ ይሆን?

በትላንትናው እለት በፈጸመችው ጥቃትም በሊባኖስ ጠቅላይ ሚንስትር ቢሮ እና በሀገሪቱ ፓርላማ አቅራቢያ ጉዳት ማድረሱ ተሰምቷልእስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ እና በዋና ከተማዋ ቤሩት ዳርቻዎች እያደረሰች ያለችው የአየር ጥቃት እየጨመረ ይገኛል፡፡በሀገሪቱ ደቡባዊ ድንበር አቅራቢያ ከጀመረችው የምድር ውግያ በተጨማሪ የምትፈጽማቸው የአየር ጥቃቶች የንጹሀን ዜጎችን ህይወት አደጋ ውስጥ ስለመክተቱ ተነግሯል፡፡ እስካሁን በድንበር አቅራቢያ የሚገኙ እና የሄዝቦላህ ጠንካራ ይዞታ መገኛ ናቸው የሚባሉ ከ20 በላይ መንደሮች ዜጎች ለቀው እንዲወጡ የእስራኤል ጦር ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም “ናባቲህ” የተባለችው የደቡባዊ ሊባኖስ ትልቅ ከተማ ነዋሪዎች ወደ ሌሎች አካባቢዎች ለመሰደድ የተገደዱ ሲሆን ትላንት የወጡ መረጃዎች በአሁኑ ወቅት በአጠቃላይ ከ1.2 ሚሊየን በላይ ሊባኖሳውያን ከቀያቸው መፈናቀላቸውን አመላክተዋል፡፡ በዚህም ምንም እንኳን ቴልአቪቭ የተገደበ ወታደራዊ ዘመቻ በሊባኖስ እንደምታደርግ ብታስታውቅም የአየር ጥቃቶቿ እያደረሱ የሚገኙት ጉዳቶች ጦርነቱን ከጋዛው ጦርነት ጋር እንዲስተካከል ሊያርግ ይችላል በሚል ከፍተኛ ስጋት አንዣቧል፡፡አጃንስ ፍራንስ ፕረስ በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ የእስራኤል ወታደሮች የጀመሩት ውግያ ቀጠናዊ ግጭትን ሊያስከትል እንደሚችል ከሚፈራው እኩል በሌሎች የሊባኖስ አካባቢዎችም ሊስፋፋ እንደሚችል ከፍተኛ ስጋት መፍጠሩን ዘግቧል፡፡የምድር ውግያው የተገደበ እንደሆነ ቢነገርም ቴልአቪቭ በአየር የምትፈጽማቸው ጥቃቶች መበራከት ሌላው የጦርነቱን ግዝፈት የሚወስን ነጥብ እንደሆነ ነው የተገለጸው፡፡በትላንትናው እለት በቤሩት የጠቅላይ ሚንስትሩ ጽህፈት ቤት እና በሀገሪቱ ፓርላማ አቅራቢያ በሚገኝ የመኖርያ ህንጻ ላይ በደረሰው ጥቃት 9 ሰዎች ሲገደሉ ከሟቾቹ መካከል ሰባቱ ከሄዝቦላህ ጋር ግንኙነት የነበራቸው ግለሰቦች እንደነበሩ ታውቋል፡፡ ከዚህ ባለፈ እስካሁን 200 የሄዝቦላህ ኢላማዎች ላይ ጥቃት መፈጸሙን ያስታወቀው የእስራኤል ጦር 9 ወታደሮቹ ሲገደሉበት 15 የቡድኑን ታጣቂዎች መግደሉን ይፋ አድርጓል፡፡  ከሰሞኑ በደረሱ የአየር ጥቃቶች በአለም አቀፍ ህግ የተከለከለውን “ዋይት ፎስፈረስ” ተቀጣጣይ ኬሚካል እስራኤል ተጠቅማለች ሲል የሊባኖስ መንግስት ከሷል፡፡ይህ ኬሚካል ህንጻዎች በቶሎ እንዲቀጣጠሉ እና በቃጠሎው ትንሽም ቢሆን ጉዳት የደረሰበት ሰው የሰውነት አካላቶቹ መስራት እንዲያቆሙ የሚያደርግ አደገኛ ኬሚካል ነው ተብሏል ፡፡ከደቡባዊ ሊባኖስ እስከ ዋና ከተማዋ ቤሩት ድረስ የተለያዩ ጠንካራ ይዞታዎች እንዳሉት የሚነገርለትን ሄዝቦላህ አቅም ለማዳከም እየተደረገ የሚገኝው ውግያ መቋጫው በምን አይነት መንገድ ሊሆን እንደሚችል ለማወቅ ከባድ ነው ተብሏል።የእስራኤል ጦር የእግረኛ ወታደሩን ድንበር አሻግሮ ሲያስገባ ውግያው ትኩረቱን የሚያደርገው የሄዝቦላ ዋሻዎችን ፣ መሰረተ ልማቶችን እና ሌሎች ቡድኑ በሚገኝባቸው አካባቢዎች ብቻ እንደሆነ አስታውቆ ነበር፡፡