October 4, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

ጅቡቲ የታጁራ ወደብን ኢትዮጵያ እንድታስተዳድር እንደምትፈቅድ አስታወቀች

ሀገሪቷ ይህን ያለችው በአፍሪካ ቀንድ እያየለ የመጣውን ውጥረት ለመቀነስ በሚል ነው

የታጁራ ወደብ ከኢትዮ ጂቡቲ ድንበር 100 ኪሜ ርቀት ላይ ይገኛል

ጅቡቲ የታጁራ ወደብን ኢትዮጵያ እንድታስተዳድር ፈቃደኛ መሆኗን ገለጸች፡፡ 

የሀገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚንስትር አሊ የሱፍ ኢትዮጵያ ከድንበር 100 ኪሎሜትር ርቀት ላይ የሚገኝውን ወደብ እንድታስተዳድር ፈቃደኛ መሆኗን ተናግረዋል፡፡ 

ሚንስትሩ ከቢቢሲ ፎከስ ኦን አፍሪካ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ እንደተናገሩት በሶማሊላንድ እና ኢትዮጵያ መካከል የተፈረመውን የወደብ ስምምነት ተከትሎ በቀጠናው እያየለ የመጣውን ወጥረት ለመቀነስ ጅቡቲ ውሳኔውን ተግባራዊ ለማድረግ ፈቃደኛ ነች ፡፡

የሀገሪቱ ፕሬዝደንት እስማኤል ኦማር ጌሌ በሰሜናዊ ክፍል የሚገኘው ወደብ ማስተዳደር እና አዲስ የተገነባ ኮሪደር መጠቀምን የሚያካትት ሀሳብ ለኢትዮጵያ መንግስት ሃሳብ አቅርበዋል ያሉት የውጭ ጉዳይ ሚንስትሩ ለማን እና መቼ ሀሳቡ እንደቀረበ ዝርዝር ሁኔታዎችን ከመግለጽ ተቆጥበዋል፡፡

ሀሳቡ በመጪው ሳምንት በቻይና በሚደረገው የቻይና አፍሪካ ትብብር ጉባኤ ላይ በዝርዝር እንደሚመረክበት ጠቁመው የሶማሊያ እና የኢትዮጵያ መሪዎች ቀጥታ ሊገናኙ የሚችሉበት እድል ስለመኖሩም አንስተዋል፡፡

የወደቡ ግንባታ አጠቃላይ 90 ሚሊየን ዶላር የፈጀውን የታጁራ ወደብ ኢትዮጵያ መጠቀም የጀመረችው ከአራት አመታት በፊት ሲሆን የኖራ ዲንጋይ ፣ ፖታሽ እና የብረት ማዕድናትን ወደ ውጭ ገበያ የምታቀርብበት ነው፡፡ 

ኢትዮጵያ በቀጠናው እያደገ የመጣውን የሀያላን ሀገራት ተሳትፎ ለመቋቋም እና የህዝቧን ደህንነት ለማስጠበቅ ራሷ የምታስተዳድረው ወደብ እንደሚያስፈልጋት ባለፉት አመታት በመንግስቷ በኩል ስተግልጽ ቆይታለች፡፡

በዚህም ከሶማሊላንድ ጋር በተፈራረመችው የወደብ የመግባብያ ስምምነት በኤደን ባህረ ሰላጤ በምታገኝው ወደብ የባህር ሀይል እና ተጨማሪ የንግድ ወደብ ለመገንባት አቅዳለች፡፡

ይህን ስምምነት ያስቆጣት ሶማሊያ አዲስአበባ ከሀርጌሳ ጋር የተፈራረመችው ስምምነት ሉአላዊነቴን ይጋፋል በሚል በወሰደቻቸው ተከታታይ እርምጃዎች ከኢትዮጵያ ጋር ዲፕሎማሲያዊ ቅራኔ ውስጥ ገብተዋል፡፡

ከሰሞኑ ሶማሊያ ከግብጽ ጋር የተፈራረመችውን የወታደራዊ ስምምነት ተከትሎም የግብጽ ወታደራዊ አውሮፕላኖች በሞቃዲሾ መታየታቸውን ተከትሎም ኢትዮጵያ ቀጠናውን ወደ ውጥረት ውስጥ እየከተቱ ናቸው ያለቻቸውን አካላት ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡ ጠይቃለች፡፡

AL AIN