October 4, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

የግብርናው ዘርፍ ሪፎርም የምግብ ዋስትናን የሚያረጋግጥ ለውጥ ማምጣቱ ተገለጸ

በግብርናው ዘርፍ በተደረገው ሪፎርም የምግብ ዋስትናን የሚያረጋግጡ ሥራዎች ተጨባጭ ለውጥ ማምጣታቸውን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ።አቶ ተመስገን “የግብርናውን ዘርፍ እምቅ አቅም እንጠቀም” በሚል መሪ ሐሳብ ዛሬ መካሄድ የጀመረውን ሀገር አቀፍ የግብርና ኢንቨስትመንት ፎረም ከፍተዋል፡፡በዚሁ ወቅትም ኢትዮጵያ ለግብርና ሥራ ተስማሚ አየርና ከባቢ እንዳላት ገልጸው÷ የግብርናውን ዘርፍ በልዩ ትኩረትና ዘመናዊ አሠራር ደግፎ ውጤት ለማምጣት መንግሥት እና አርሶ አደሩ በቁርጠኝነት እየሠሩ ነው ብለዋል፡፡በዘርፉ ፈጣንና ቀላል አሠራሮችን በዘመነ መንገድ ለማከናወን የተጀመሩ ውጤታማ ሥራዎች መኖራቸውን ጠቅሰው÷ የውጭ ኢንቨስተሮችም ከኢትዮጵያ ጋር እንዲሠሩ ጥሪ አቅርበዋል፡፡የግብርና ሚኒስትር ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) ኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ በተገበረችው ሪፎረም ከራሷ አልፎ ምርቶችን ወደ ውጭ መላክ መጀመሯን አንስተው÷ ውጤቱም የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን እያበረታታ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡የምግብ ሉዓላዊነት ላይ የሚተገበሩ ተነሳሽነቶችና ፕሮጀክቶች ሳይቆራረጡ ተግባራዊ መሆን እንዳለባቸው ያመላከቱት ደግሞ የዓለም ምግብና እርሻ ድርጅት (ፋኦ) ዋና የኢኮኖሚ አማካሪ ማክሲሞ ቶሬሮ (ዶ/ር) ናቸው፡፡ኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ እያሳየች ያለውን ውጤት አድንቀው÷ ድርጅታቸው ኢትዮጵያን ጨምሮ በተለያዩ ሀገራት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የግብርናና ኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶችን በትኩረት ይሰራል ብለዋል፡፡

FBC