October 4, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ አቅምን አሟጥጦ መጠቀም እንደሚገባ ተገለጸ

የኢትዮጵያን የምግብ ሉዓላዊነት የማረጋገጥ ተልዕኮን ከግብ ለማድረስ አቅምን አሟጥጦ መጠቀም እንደሚገባ ግብርና ሚኒስቴር አስገነዘበ፡፡

የሚኒስቴሩ የ2016 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈፃፀምና የ2017 ዕቅድ የጋራ ምክክር በአሶሳ ከተማ መካሄድ ጀምሯል፡፡

የግብርና ሚኒስትር ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) ግብርና ከተሰጠው ትኩረት ጋር ተያይዞ ዘርፉን ከማዘመን ጀምሮ ምርታማነትን በማሳደግ፣ በአረንጓዴ ዐሻራ፣ የደን ሽፋንን በማሳደግ፣ በሌማት ትሩፋት፣ የወጪ ንግድ ምርቶችን በመጨመር እና ሌሎች ተግባራት የተመዘገቡ ውጤቶች አበረታች መሆናቸውን አብራርተዋል፡፡

እየተመዘገቡ ያሉ ስኬቶች እንደተጠበቁ ሆነው÷ እንደ ሀገር የሚጠበቅብንን የኢትዮጵያን የምግብ ሉዓላዊነት የማረጋገጥ ተልዕኮ ከግብ ለማድረስ አሁንም አቅማችንን አሟጥጠን መሥራት እና ለስኬታማነት መፍጠን ይጠበቅብናል ብለዋል፡፡

የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መሥተዳድር አሻድሊ ሀሰን በበኩላቸው÷ የተጀመሩ የልማት ተግባራትን በስኬት በመፈጸም የሕዝብን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በቅንጅት ባደረግነው ጥረት ውጤቶች ተመዘግበዋል ብለዋል፡፡

መድረኩ በዘርፉ የሚስተዋሉ ውስንነቶችን ለመፍታት፣ የታዩ ጥንካሬዎችና ስኬቶች የበለጠ አጠናክሮ ለማስቀጠል የሚያልስችል ተግባቦት የሚፈጠርበት እንደሚሆንም ጠቁመዋል፡፡

FBC