October 4, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

በክልሉ የተጀመረውን የኮሪደር ልማት አጠናክሮ ለማስቀጠል የተቀናጀ ርብርብ ያስፈልጋል – አቶ ጥላሁን ከበደ

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የተጀመረውን የኮሪደር ልማት ስራ አጠናክሮ ለማስቀጠል የተቀናጀ ርብርብ እንደሚያስፈልግ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ የኮሪደር ልማት ስራን በክልሉ በሚገኙ ሁሉም ከተሞች ተግባራዊ ማድረግ በሚያስችሉ ጉዳዮችና የዝግጅት ሂደት ላይ ያተኮረ ውይይት በአርባምንጭ ከተማ እያካሄዱ ነው። አቶ ጥላሁን ከበደ በዚህ ወቅት፣ ከተሞች ለነዋሪዎቻቸው ምቹና የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ የኮሪደር ልማት ስራን አጠናክሮ መቀጠል ይገባል ብለዋል። የተሻለ ከተማ ለቀጣይ ትውልድ ለማስረከብ እየተደረገ ላለው ሂደት የኮሪደር ልማት ስራ ትልቅ ድርሻ እንዳለው ጠቅሰው፤ ለዚህም የከተማ ነዋሪዎችና የስራ አመራሩ ቁርጠኝነት እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። በውይይቱ የክልሉ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት እየተሰተፉ መሆኑን ከክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።