በትምህርት ስራ ላይ ያሉ አመራሮች የትምህርትን ሥራ ከፖለቲካ በመለየት በትምህርት ስራው ላይ ብቻ ማተኮር እንዳለባቸው የትምህርት ሚኒስትሩ ብርሃኑ ነጋ (ፕ/ር) ገለጹ።
ሚኒስትሩ በ33ኛው ሀገር አቀፍ የትምህርት ጉባዔ ላይ እንደገለጹት÷ በትምህርት ስራ የሚፈለገው ውጤት እንዲመጣ የዘርፉ አመራሮች ትምህርትና ፖለቲካን መቀላቀል የለባቸውም።
የትምህርት አመራሮች ዋነኛ ስራ የትምህርትና የፖለቲካ ስራን ሳይቀላቅሉ በቅንነትና በሀቀኝነት ማገልገል እንደሆነ ገልጸዋል።
ትምህርትን በጥራትና በፍትሃዊነት ለዜጎች ለማቅረብ ለተጀመረው ስራ ስኬት የትምህርት ስራ ባለድርሻዎች ጠንክሮ መሥራት እንደሚጠበቅባቸውም ጠቁመዋል።
የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ወ/ሮ አየለች እሸቴ በበኩላቸው÷ የትምህርት ጥራት፣ ፍትሀዊነትንና ተገቢነቱን ለማረጋገጥ የሚሰራውን ስራ ውጤታማ ለማድረግ የመምህራንን አቅም ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል።
የመምህራንን የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ከክልሎች ጋር በመነጋገር ለመፍታት እየተሞከረ ያለው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል።
የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ስራዎቻቸውን በቁልፍ የአፈጻጸም አመላካቾች በመለካት ለተሻለ ስራ መትጋት እንዳለባቸው የገለጹት ደግሞ ሌላው የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ኮራ ጡሹኔ ናቸው፡፡
በጉባኤው የክልል ትምህርት ቢሮ ኃላፊዎች፣ የዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንቶች፣ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ የሙያ ማህበራትና አጋሮች እየተሳተፉ መሆኑን የሚኒስቴሩ መረጃ ያመላክታል፡፡
FBC
More Stories
በ2016 የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የ8 ነጥብ 1 በመቶ ዕድገት አስመዝግቧል- ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር)
ሙስና የተበላሸ አስተሳሰብ፣ ባህልና አሰራር ውጤት ነው – ም/ጠ/ሚ ተመስገን ጥሩነህ
የሸካ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤቶች የ2017 በጀት ዓመት የዳኞች መደበኛ ስራ የማስጀመሪያ ውይይት መድረክ በማሻ ከተማ አካሂዷል።