October 4, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

በጅማ ዞን ሁለት ወረዳዎች የመሬት መንሸራተት ስጋት ያለባቸውን ነዋሪዎች ወደ ሌላ ቦታ ማስፈር ተጀመረ

በኦሮሚያ ክልል ጅማ ዞን ሁለት ወረዳዎች የመሬት መንሸራተት አደጋ ስጋት ያለባቸው ነዋሪዎች ጉዳት እንዳይደርስባቸው ወደ ሌላ ቦታ የማስፈር ስራ መጀመሩን የዞኑ ቡሳ ጎኖፋ ጽህፈት ቤት ገለጸ።

በዞኑ በአንዳንድ ወረዳዎች ከባለፈው ዓመት ጀምሮ የመሬት መንሸራተት አደጋ በመከሰቱ የቅድመ ጥንቃቄ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑንም ጽህፈት ቤቱ ገልጿል።

የጽህፈት ቤቱ ሃላፊ ወ/ሮ ፍጹም ጌታሁን፤ ሰሞኑን በጣለው ከባድ ዝናብ ምክንያት ጎማ እና ጌራ ወረዳዎች የተለያዩ ቀበሌዎች ላይ የመሬት መንሸራተት አደጋ መከሰቱን ተናግረዋል።

አደጋው ሰፍቶ የሰው ህይወት ላይ ጉዳት እንዳያደርስ የቅድመ መከላከል ስራ መጀመሩን ገልጸው፤ ነዋሪዎችን ወደ ሌላ ቦታ የማስፈር ስራ መጀመሩን መግለጻቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

በዚሁ መሰረት በጌራ ወረዳ 591 ነዋሪዎችን እንዲሁም ከጎማ ወረዳ 330 ነዋሪዎችን ለመሬት መንሸራተት አደጋ ተጋላጭ ከሆኑ አካባቢዎች ተነስተው ወደ ሌላ ቦታ የማስፍር ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል።

ከነዚህ ወረዳዎች በተጨማሪ በሰቃ ጨቆርሳ፣ በሸቤ ሶምቦ፣ በሰጠማና በነዲ ጊቤ ወረዳዎች የመሬት መንሸራተት ስጋት ያለባቸው አካባቢዎች ላይ የቅድመ መከላከል ስራ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

በቀጣይም የአደጋው ተጋላጮችን ከቦታው የማራቅ እና አደጋው የደረሰባቸውን ደግሞ መልሶ የማቋቋም እና የመደገፍ ስራ በቅንጅት እንደሚሰራ አክለዋል።

FBC