October 4, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

የብሔራዊ አቢይ ኮሚቴ መግለጫ

የብሔራዊ አቢይ ኮሚቴ መግለጫOn Aug 12, 2024 1,049በአማራ እና ትግራይ ክልሎች መካከል የይገባኛል ጥያቄ የሚነሳባቸውን አከባቢዎች ጉዳይ በፕሪቶሪያው ስምምነት አግባብና በህገመንግስቱ መሰረት ዘላቂ እልባት ለመስጠት የተጀመረው እንቅስቃሴ ስኬታማ መሆኑን ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት የተቋቋመው ብሔራዊ አቢይ ኮሚቴ አስታወቀ፡፡ብሔራዊ አቢይ ኮሚቴው በዛሬው ዕለት ማለትም ነሐሴ 6/2016 ዓ.ም ለዚሁ ዓላማ የተቋቋመው የቴክንክ ኮሚቴ አባላት በተገኙበት በአዲስ አበባ ስብሰባውን አካሂዷል።ኮሚቴው ከዚህ ቀደም ባደረገው ስብሰባ በበርካታ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ሰፊ እና ጥልቀት ያለው ውይይት ካደረገ በኋላ ባለ 13 ነጥብ የማስፈፀሚያ አቅጣጫዎችን በማስቀመጥ ወደ ትግበራ ተገብቶ እንደነበር ይታወሳል።በዛሬው ቀን አቢይ ኮሚቴው ባካሄደው ስብሰባም በቀዳሚነት የእስካሁኑን አፈፃፀም ገምግሟል። ለዚሁ ዓላማ የተቋቋመው የቴክኒክ ኮሚቴም በራያ እና በፀለምት አካባቢዎች ተፈናቃዮችን ከመመለስ አኳያ የተሰሩ ስራዎች ሪፖርት በዝርዝር ለብሔራዊ ኮሚቴው አቀርቦ ጥልቅ ውይይት ተደርጎበታል።ለብሔራዊ አብይ ኮሚቴው ከቀረበው ሪፖርት እና በተጨባጭም መሬት ላይ ከተሰሩት ሥራዎች መረዳት እንደተቻለው የእስካሁ የትግበራ ምዕራፎች እጅግ ስኬታማና መሬት ላይ ውጤት የታየባቸው መሆናቸው ተገምግሟል። በዚህ መሰርት ከራያ እና ከፀለምት ተፈናቅለው የነበሩ ዜጎች ወደ ቀድሞ አካባቢያቸው እንዲመለሱ የተደረገ ሲሆን ለዚህ ስኬት የአማራ እና የትግራይ ክልል አመራሮች አወንታዊና ሚና እንደነበራቸውና ችግሮችን ተቋቁመው ለስኬት ለመድረስ ብርቱ ጥረት ማድረጋቸውን አብይ ኮሚቴው ገምግሟል። በተለይም የሀገር መከላከያ ሰራዊት ሂደቱን በመምራት እና በማስፈፀም ረገድ የነበረው ሚና እጅግ ከፍተኛ ሲሆን ለስኬቱም የነበረውን ወሳኝ ድርሻ ብሔራዊ አብይ ኮሚቴው አድንቋል። የፌደራል የፀጥታ ተቋማት በተለይም የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት እና የፌደራል ፖሊስ ሂደቱ እንዲሳካ የነበራቸው ገንቢ ሚናም በብሔራዊ ኮሚቴው ምስጋናና እውቅና ተችሮታል።ተፈናቃዮችን በመመለስ ሂደት ውስጥ በህዝቦች መካከል የታየው ኢትዮጵያዊ ባህል፣ አንድነት፣ ፍቅር እና መተሳሰብ ከምንም በላይ ዋጋ የሚሰጠው መሆኑ በተግባር መረጋገጡን ያስታወቀው የአቢይ ኮሚቴው መግለጫ በተመላሽ ተፈናቃዮችም ከቀየው ሆኖ በቆየው ህዝብም መካከል የነበረው መነፋፈቅና ስስት ሁሉንም ዓይነት እንቅፋትና አዳናቃፊችግር የተሻገረና ለስኬቱ ወሳኝ ሚና የነበረው እንደነበረ አባራርቷል፡፡ ሂደቱ ኢትዮጵያዊ አንድነታችን ከምንም በላይ ሥር የሰደደና ከፍ ያለ መሆኑንን በተጨባጭ ያስመሰከረ መሆኑንም አብይ ኮሚቴው ገምግሟል።በመከላከያ ሰራዊቱ፣ በሁለቱ ክልሎች እና በፌዴራል መንግስት ለተሰራው ስኬታማ ሥራ የህዝባች ድጋፍ ሂደቱ እንዲፋጠን እና እንዲሳለጥ በማድረግ በኩል እጅግ ከፍ ያለ ሚና እንደነበረውና ለቀጣይ ሥራዎች ዋስትና እንደሆነም ተገምግሟል።በሌላ በኩል ተፈናቃዮችን የመመለስ ሥራው እንዳይሳካ ከሁለቱም ክልሎች በኩል የማስተጓጎል ሚናን ሲጫወቱ የነበሩ አካላት እንደነበሩ የጠቆመው አቢይ ኮሚቴው አደናቃፊዎቹ ከመንግስት እና ከህዝቡ ፍላጎትና አቅም በታች በመሆናቸው የታለመው ስኬት ሊመዘገብ እንደቻለ መግባባት ላይ ተደርሶበታል። በተጨማሪም በራያ እና በጠለምት ተፈናቃዮችን የመመለስ ሥራው ለቀጣይ ሥራዎች ልምድ የተወሰደበት እና ብርታትን የሚሰጥ በመሆኑ የተንጠባጠቡ ጉዳዮች በተጀመረው መተማመንና ቁርጠኝነት ከሥር ከሥር እየተፈቱ ወደጊዜያዊ አስተዳደር የማስመረጥ ሥራው ዝግጅት በፍጥነት መሸጋገርና የራያና ፀለምትን ልምድ በመቀመር የቀሩ ተፈናቃዮችን የመመለስ ጅምሩን ለመቋጨት መረባረብ እንደሚገባም አቅጣጫ ተቀምጧል።በዚህም መሰረት በመከላከያ አስተባባሪነት ፣ ፌዴራል መንግስት በሚመድባቸው ሲቪል አመራሮች እገዛ እና በሁለቱ ክልሎች ታዛቢነት፣ በህዝቡ ሙሉና ቀጥተኛ ተሳትፎ ህዝቦች የራሳቸውን ጊዜያዊ የአካባቢ አስተዳደር እንደሚመርጡ ብሔራዊ አቢይ ኮሚቴው አቅጣጫ አስቀምጧል። ይህም ህዝቡ እራሱ ይሆነኛል ያለውን አስተዳደር እንዲመሰርት የሚረዳው ከመሆኑም በተጨማሪ አካባቢዎቹ ዘላቂ መፍትሔ እስኪያገኙ ድረስ ወደ መደበኛው የአስተዳደራዊ ስርዓት እንዲመለሱ እንደሚያግዝ ተመላክቷል። በዚህ መሰረት አካባቢያዊ አሰተዳደራዊ መዋቅር የመመስረት ሂደቱ በአስቸካይ ተፈፃሚ እንዲሆን አቅጣጫ መቀመጡን ብሔራዊ አቢይ ኮሚቴው የላከው መግለጫ ያመለክታል።

FBC