October 5, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

በአስቸኳይ የሙስና መከላከል ሥራ 2 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር ከምዝበራ ማዳን ተቻለ

 በ2016 በጀት ዓመት በአስቸኳይ የሙስና መከላከል ሥራ ከ2 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር በላይ ከሙስና እና ከምዝበራ ማዳን መቻሉን የፌደራል የስነ-ምግባር እና ፀረ ሙስና ኮሚሽን አስታወቀ ።

በኮሚሽኑ የአስቸኳይ ሙስና መከላከል መሪ ሥራ አስፈፃሚ አቶ ገዛኸኝ ጋሻው÷ በ2016 በጀት ዓመት በተከናወኑ አበይት ጉዳዮች ዙሪያ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።

በመግለጫቸውም÷ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ175 ሺህ በላይ አመራርና ሰራተኞች ሃብታቸውን ማስመዝገባቸውን አንስተዋል፡፡

በክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች 1 ሺህ 87 አስቸኳይ የሙስና መከላከል ሥራ መከናወኑን ነው የተናገሩት፡፡

በዚህም 2 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር እና 8 ሺህ 490 የአሜሪካ ዶላር ማዳን መቻሉን ጠቁመው÷ ከመሬት ጋር በተያያዘም ከ46 ሚሊየን ካሬ ሜትር የከተማና የገጠር ቦታ ከሙስና ምዝበራ ማዳን ተችሏል ብለዋል፡፡

አስቸኳይ የሙስና መከላከል ሥራው ከግዥ፣ መሬት አሰጣጥ፣ ንብረት ማስወገድ፣ ገቢ አሰባሰብ ፣ ዕርዳታ አሰጣጥ እና ከማዳበሪያ ስርጭት ጋር የተያያዘ እንደሆነ መጥቀሳቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

FBC