July 7, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

የፌዴራል ፖሊስ ከናይጄሪያ የጦር ኮሌጅ ጋር የልምድ ልውውጥ አደረገ

 የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ከናይጄሪያ ፌዴራል ሪፐብሊክ የጦር ኮሌጅ ጋር “የማዕድን ዘርፍን መጠበቅ ለተጠናከረ ብሔራዊ ደህንነት” በሚል ርዕስ የልምድ ልውውጥ አድርጓል፡፡

በልምድ ልውውጡ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጄነራል ደመላሽ ገ/ሚካኤል ÷ ኢትዮጵያ በርካታ ማዕድናት እንዳላት በመግለጽ የመንግስት ፖሊሲና መመሪያ በመሻሻሉ ምክንያትም ለልማት ከፍተኛ አቅም መፍጠሯን ገልፀዋል።

ኢትዮጵያ በሀገርና በዓለም አቀፍ ደረጃ ለማዕድን አምራች ባለሃብቶች ማራኪ መዳረሻ መሆኗን ጠቅሰዋል፡፡

ሀብቶችን ከሕገ-ወጥ ብዝበዛና ከሕገ-ወጥ ዝውውር መጠበቅ ለሀገር ደኅንነት ወሳኝ ሚና እንዳለውም አንስተዋል፡፡

ሕገ-ወጥ የማዕድን ሥራ ግጭትን እንዳያባብስ፣ የተደራጁ ወንጀሎችን ተጠናክረው በአካባቢው ማህበረሰብ ሕይወት ላይ ተጽዕኖ እንዳያሳድሩ ፖሊስ ለዘርፉ ትልቅ ትኩረት በመስጠት ኃላፊነት ያለው አስተዳደር ለማረጋገጥ እየሠራ እንደሚገኝም ተናግረዋል፡፡

በናይጄሪያ የፌደራል ሪፐብሊክ ጦር ኮሌጅ አዛዥ ሜጀር ጀነራል አይቢ ማይና የተመራው ልዑካን ቡድን የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ የቴክኖሎጂ አቅሞችን ተዘዋውሮ መጎብኘቱን ከፌዴራል ፖሊስ ገጽ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

FBC