July 4, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

ዳያስፖራው በሕጋዊ መንገድ ከሚልከው ገንዘብ በየዓመቱ በአማካይ ከ4 እስከ 5 ቢሊዮን ዶላር እየተገኘ ነው

ዳያስፖራው በሕጋዊ መንገድ ከሚልከው ገንዘብ (ሬሚታንስ) ባለፉት 5 ዓመታት በየዓመቱ በአማካይ ከ4 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱን የኢትዮጵያ ዳያስፖራ አገልግሎት አስታወቀ።

በተጨማሪም ዳያስፖራው ለሀገራዊ ጥሪዎችና የልማት ስራዎች እያደረገ ያለው ተሳትፎ እያደገ መምጣቱ ተገልጿል።

የ2016 በጀት ዓመት ከመጠናቀቁ በፊት የመጨረሻ የሆነው የሚኒስትሮች ምክር ቤት የ100 ቀናት ግምገማ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት ትናንት ተጀምሯል።

የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር) በዚሁ መድረክ ያለፉት 100 ቀናትና የሁለተኛው ሀገር በቀል ኢኮኖሚ አፈጻጸም ሪፖርት እንዲሁም የ2017 በጀት ዓመት የትኩረት አቅጣጫዎችን አቅርበዋል።

በሪፖርታቸው፥ በ2016 በጀት ዓመት 10 ወራት ዳያስፖራው በሕጋዊ መንገድ ወደ ሀገር ቤት ከላከው ገንዘብ (ሬሚታንስ) 4 ነጥብ 2 ቢሊዮን ዶላር መገኘቱን ገልጸዋል።

በዚህ ዙሪያ ኢዜአ ያነጋገራቸው የኢትዮጵያ ዳያስፖራ አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር በላይነህ አቅናው ከዳያስፖራው በሕጋዊ መንገድ ወደ ሀገር ቤት የሚላከው የውጭ ምንዛሬ የተሻለ እድገት ማሳየቱን ገልጸዋል።

ባለፉት 5 የለውጥ ዓመታት ዳያስፖራው በየዓመቱ በአማካይ ከ4 እስከ 5 ቢሊዮን ዶላር እየላከ እንደሆነ አመልክተዋል።

ከዳያስፖራው እየተገኘ ያለው ገቢ ከለውጡ በፊት ከሚገኘው የውጭ ምንዛሬ አንጻር ከፍተኛ እድገት ያለው መሆኑን ጠቅሰው፤ እድገቱ የዳያስፖራውን ተሳትፎ ለማስፋት በተከናወኑ የማሻሻያ ስራዎች የተገኘ ነው ብለዋል።

FBC