July 4, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

ጠ/ሚ ዐቢይ (ዶ/ር) በተገኙበት ሁሉም ባለድርሻ አካላት የሚሳተፉበት ሀገር አቀፍ ምክክር ተጀመረ

የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን በሀገር አቀፍ ደረጃ ሁሉም ባለድርሻ አካላት የሚሳተፉበትን የምክክር ምዕራፍ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት አስጀምሯል።በዓድዋ ድል መታሰቢያ በተጀመረው ሀገር አቀፍ የምክክር ምዕራፍ ላይም÷ የሕብረተሰብ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የሦስቱ የመንግስት አካላት (ሕግ አውጪ፣ ሕግ አስፈጻሚና ሕግ ተርጓሚ)፣ የተቋማትና የማኅበራት ተወካዮች እንዲሁም ተፅዕኖ ፈጣሪ ግለሰቦች ተሳትፈዋል፡፡የኮሚሽኑ ዋና ኮሚሽነር መስፍን አርዓያ (ፕ/ር) በመድረኩ ላይ እንዳሉት÷ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን በርካታ ፈተና ቢገጥመውም ሳይበገር መቀራረብንና መግባባትን ለማምጣት እየሰራ ነው ብለዋል፡፡እስከ አሁን በ10 ክልሎችና በሁለት ከተማ አስተዳደሮች ከ1 ሺህ በሚልቁ ወረዳዎች በአጀንዳ ማሰባሰብ የምክክር ምዕራፍ ሂደት የሚሳተፉ ተወካዮች ማስመረጥ መቻሉን ጠቁመው÷ በአዲስ አበባ የአጀንዳ መሰብሰብ ስራ መጀመሩን አስታውቀዋል፡፡በቀጣይም የተሳታፊዎች መረጣ በተካሄደባቸው ክልሎችና በድሬዳዋ ከተማ አጀንዳ እንደሚሰበሰብ አስረድተው÷ በአማራና ትግራይ ክልሎች ደግሞ የተሳታፊዎች ልየታና መረጣ እንደሚካሄድ አመላክተዋል፡፡ኮሚሽኑ የአሁኑ ወጣት ትውልድ ከቀደሙት ትውልዶች ብዙ ተምሮ የተሻለ የሰላምና የእድገት ውርስ ይተዋል የሚል እምነት እንዳለውም ገልጸዋል፡፡“ከስብራት ሕይወት ወጥተን ወደ ተሻለ ሕይወት እንሸጋገር ዘንድ ወጣቱ ችግሩን በአጀንዳ ቀረፃ ጠብመንጃውን ወደ ሐሳብ መንጃና ማንሸራሸሪያ እንዲቀይር ኮሚሽኑ በትህትና ይጠይቃል” ብለዋል፡፡የሀገራችንን ችግር ወደ ሀገራዊ መፍትሔ ለማምጣት ኮሚሽኑ በምክክር ሂደት የሰላም በር በየትኛውም ቦታ ላሉ ወገኖች እንዲመቻች ጠንክሮ እንደሚሰራ ማረጋገጣቸውን የኮሚሽኑ መረጃ አመላክቷል፡፡በተጀመረው የአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደት ማንኛውም ኢትዮጵያዊ አጀንዳውን በግልም ሆነ በጋራ ወደ ኮሚሽኑ ማምጣት እንደሚችል ገልጸው÷ ምክክሩ አካታች እንደሚሆንና ሂደቱም ግልፅና ተዓማኒ በሆነ መልኩ እንደሚከናወን አስረድተዋል፡፡

FBC