July 2, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

ለችግሩ መፍትሄ ማስቀመጥ እንጂ ከዲጂታል ፋይናንስ ሲስተም ውጭ መሆን አይቻልም- ብሔራዊ ባንክ

ዲጂታል ፋይናንሺያል ላይ የሚስተዋለው ወንጀል የገዘፈ መሆኑን በመገንዘብ መፍትሄ ማስቀመጥ እንጂ ከዲጂታል ፋይናንስ ሲስተም ውጭ መሆን አይቻልም ሲሉ የብሔራዊ ባንክ ገዥ ማሞ ምኅረቱ አስገነዘቡ፡፡የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ÷ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ፣ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ከግል ባንኮች ፕሬዚዳንቶች ጋር የዲጂታል ፋይናንሺያል ወንጀልን በጋራ ለመከላከል ያለመ ውይይት አካሂዷል፡፡የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገ/ሚካኤል በውይይ ላይ እንዳሉት÷ ከባንኮች ጋር ተያይዘው የሚፈፀሙ የሳይበር፣ የሞባይል ባንኪንግ እና ማህበራዊ ሚዲያን በመጠቀም የሚፈፀሙ ወንጀሎች እየተወሳሰቡና እየተበራከቱ መምጣታቸውን አስገንዝበዋል፡፡መዛሬው መድረክም ይህን በመገንዘብ በጋራ በመምከር ወንጀሉን ለመከላከልና የመፍትሄ አቅጣጫ ለማስቀመጥ ያለመ መሆኑን አስረድተዋል፡፡የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ እና የቴክኖሎጂ አቅም እያደገ ሲሄድ በዚያው ልክ ችግሩም አብሮ እንደሚያድግ ታሳቢ መደረግ እንዳለበትም አመላክተዋል፡፡ቴክኖሎጂው ሲበለጽግ በኅብረተሰቡ ላይ የሚያስከትለው ጉዳት ተለይቶ ለደንባኞች፣ ለባንክ ሠራተኞች እና ለሕግ አስከባሪው ተገቢውን ግንዛቤ መፍጠር እንደሚገባም ነው በአፅንኦት የገለጹት፡፡ቴክኖሎጂ ሲበለጽግ ፖሊስ ከባንኮች እና ከሚመለከታቸው ተቋማት መረጃ የሚያገኝበትና የሚሰጥበት አሰራር እንዲዘረጋም ጠይቀዋል፡፡የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ማሞ ምኅረቱ በበኩላቸው÷ ዲጂታል ፋይናንሺያል ላይ የሚስተዋለው ወንጀል የሰፋና የገዘፈ ችግር መሆኑን በመገንዘብ ለችግሩ መፍትሄ ማስቀመጥ እንጂ ከዲጂታል ፋይናንስ ሲስተም ውጭ መሆን እንደማይቻል ገልፀዋል፡፡የዲጅታል ፋይናንስ ወንጀልን ለመከላከልም ቴክኖሎጂ፣ የህግ ማዕቀፍ፣ ትብብርና የማህበረሰብ ንቃት ላይ የሚሰራው ስራ ችግሩን እንደሚያቃልለው ጠቁመዋል፡፡በተጨማሪም ብሄራዊ መታወቂያ መጠቀም እንደ አንድ የችግሩ ማቅለያ መፍትሄ ነው ማለታቸውን የፌደራል ፖሊስ መረጃ አመላክቷል፡፡

FBC