July 4, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

ኢትዮጵያ በአእምሯዊ ንብረት፣ በጄኔቲክ ሃብትና ተዛማጅ ማህበረሰባዊ እውቀት ዓለም አቀፍ ስምምነት ፈረመች

ኢትዮጵያ በአእምሯዊ ንብረት፣ በጄኔቲክ ሃብት እና ተዛማጅ ማህበረሰባዊ እውቀት ታሪካዊ ነው የተባለውን ዓለም አቀፍ ስምምነት ፈርማለች።

የዓለም አእምሯዊ ንብረት ድርጅት አባል ሀገራት በአእምሯዊ ንብረት፣ በጄኔቲክ ሃብት እና ተዛማጅ ማህበረሰባዊ እውቀት ላይ አዲስ ታሪካዊ ስምምነትን አጽድቀዋል።

የዓለም አእምሯዊ ንብረት ድርጅት አባል ሀገራት እ.ኤ.አ ከግንቦት 13 እስከ 24 ቀን 2024 በጀኔቭ ባካሄዱት ዲፕሎማቲክ ኮንፍረንስ ስምምነቱ መጽደቁን የአእምሯዊ ንብረት ባለስልጣን አስታውቋል።

ስምምነቱ በጄኔቲክ ሃብት እና በተዛማጅ ማህበረሰባዊ እውቀት ላይ ተመስርተው ለሚቀርቡ የአዕምሮ ፈጠራ ባለቤትነት ማመልከቻዎች አመልካቾቹ የፈጠራዎቻቸውን የዘረመል ሀብቶች እና ተዛማጅ ማህበረሰባዊ እውቀቶች መገኛ ምንጭ እንዲገልጹ የሚያስገድድ መሆኑ ተገልጿል።

በተጨማሪም የአዕምሮ ፈጠራ ባለቤትነት ሥርዓቱን ውጤታማነት ፣ ግልጽነት እና ጥራትን ለማሳደግ እንደሚረዳና በዘረመል ሀብቶች እና ተያያዥ ባህላዊ እውቀት ላይ አዲስነት ወይም ፈጠራዊ ብቃት የሌላቸው ፈጠራዎች ያለአግባብ ዕውቅና እንዳያገኙ ለመከላከልም ያስችላል ተብሏል፡፡

ኢትዮጵያን በመወከል የመጨረሻውን ሰነድ የፈረሙት የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ወልዱ ይመሰል ÷ኢትዮጵያ ስምምነቱን ስትፈርም የዘረመል ሀብቶችን እና ተያያዥ ባህላዊና ማህበረሰባዊ እውቀቶችን መጠበቅ ብቻ ሳይሆን በኃላፊነት እና በፍትሃዊነት ጥቅም ላይ የሚውሉበትን ቀጣይ ሁኔታ በመገንዘብና በማለም ነው ብለዋል፡፡

አባል ሀገራት የጋራ ቅርሶቻቸውን ለማክበር እና ለመጠበቅ የሚያደርጉትን ጥረት ስምምነቱ ይወክላል ፤ ይህም ለትውልድ የእውቀት እና የብልጽግና ምንጭ ሆኖ እንዲቀጥል ያደርጋል ሲሉ መናገራቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

ኢትዮጵያ ይህንን ስምምነት መፈጸሟ ያላትን የበለፀገ የዘረመል ሀብቷን እና ባህላዊ እውቀቷን በመጠቀም፣ ሁሉም ማህበረሰቦች ላበረከቱት አስተዋፅኦ ተገቢውን እውቅና እና ጥበቃ እንዲያገኙ ለማድረግ ያለመ መሆኑንም አያይዘው አብራርተዋል።

FBC