July 2, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

የዋጋ ግሽበት ወደ 23 ነጥብ 3 በመቶ ዝቅ ማለቱ ተገለጸ

በኢትዮጵያ ባለፉት ዘጠኝ ወራት የዋጋ ግሽበትን ከነበረበት ወደ በ23 ነጥብ 3 በመቶ ዝቅ ማድረግ መቻሉን የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡

ሚኒስትሯ በሰጡት ማብራሪያ፥ የዋጋ ንረት በተለይም ለምግብ ፍጆታነት የሚውሉ ጥሬ ዕቃዎች በየጊዜው እየጨመሩ በመሆኑ በመንግስት በኩል ቢያንስ እየጨመሩበት ያለውን መጠን ለመቀነስ እየተሞከረ እንደሆነ ጠቅሰዋል፡፡

የዋጋ ንረቱን ለማረጋጋት መንግስት ነዳጅና ማዳበሪያ ላይ የተለያዩ ድጎማዎችን እያደረገ እንደሚገኝ ተገልጿል፡፡

የኑሮ ውድነት፣ የስራ አጥ ቁጥር መጨመር፣ የውጭ ዕዳዎች አከፋፈል፣ የዓለም የፖለቲካ አቋም መለዋወጥ በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ላይ ያላቸው ተግዳሮቶች ከፍተኛ በመሆኑ በአንዳንድ ዘርፎች ላይ የታቀደውን ግብ ማሳካት አለመቻሉን ሚኒስትሯ ጠቁመዋል፡፡

የግሉ ዘርፍ ሰፊ የስራ ዕድል እንዲፈጥር በማበረታታት ትልቅ ስራ እየተሰራ ቢሆንም በበለጠ መስራት እንደሚጠበቅ ገልጸው፤ የዘርፎች ተወዳዳሪነትና ምርታማነት አሁንም ትልቅ ስራ የሚፈልግ እንደሆነም አንስተዋል፡፡

በዓለም አቀፍ ደረጃ የልማት አጋርነት መቀዛቀዝ በጎረቤትና በሌሎች ሀገራት የልማት ድጋፍ፣ የልማት አጋርነት በተለያዩ በሚያጋጥሙ ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋዎች ምክንያት በመቀዛቀዙ፣ የአቅርቦት ሰንሰለት መቆራረጡ ከፍተኛ የሆነ ተግዳሮት በመሆኑ በሀገሪቷ ኢኮኖሚ ላይ ጫና ፈጥሯልም ብለዋል፡፡

FBC