የኢራኑ መንፈሳዊ መሪ አያቶላህ አሊ ሃሚኒ ሞሃማድ ሞክበርን የኢራን ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት አድርገው ሾመዋል፡፡ሞሃማድ ሞክበር በሄሊኮፕተር አደጋ ሕይወታቸው ያለፉት ፕሬዚዳንት ኢብራሂም ራይሲ ምክትል እንደነበሩ ይታወሳል፡፡በተመሳሳይ አደጋ ሕይወታቸው ያለፉት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሆሴን አሚር አብዱላሂን በመተካት ደግሞ አሊ ባጌሪ ካኒ የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሆነው ተሾመዋል፡፡አሊ ባጌሪ ካኒ ቀደም ሲል የኢራን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በመሆን ሲያገለግሉ እንደነበር ተመላክቷል፡፡በኢራን ከ50 ቀናት በኋላ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ እንደሚካሄድ መገለጹንም አልጀዚራ በዘገባው አስፍሯል፡፡በተያያዘ ዜና በሄሊኮፕተር አደጋው ለደረሰው ሀዘን የተለያዩ ሀገራት ለኢራን ህዝብና መንግስት መጽናናትን ተመኝተዋል።በዚህም የሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን፣ የደቡብ አፍሪካው ፕሬዚዳንት ሲሪል ራማፎዛ፣ የህንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ፣ የፓኪስታኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ሼሃባዝ ሻሪፍ ይገኙበታል፡፡በተጨማሪም የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች ፕሬዚዳንት ቢን ዛይድ አል ናህያን እና የቬንዝዌላው ፕሬዚዳንት ኒኮላስ ማድሮ እና በርካታ የሀገራት መሪዎች ሀዘናቸውን ገልጸዋል።
FBC
More Stories
የዩክሬን አየር ሃይል 106 የሩሲያ ሰው አልባ አውሮፕላኖችን መትቶ መጣሉን አስታውቋል፡፡
ትራምፕ ጦርነቱን በመጀመር እና ስምምነት ላይ ባለመድረስ ዩክሬንን ወቀሱ
ሩሲያ በዩክሬን ጦርነት ጉዳይ ንግግር ለመጀመር አጥጋቢ እቅድ እንዳልደረሳት ገለጸች