July 7, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

ጠ/ሚ ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በ#ጽዱኢትዮጵያ ንቅናቄ ለተሳተፉ ሁሉ ምስጋና አቀረቡ

በ#ጽዱኢትዮጵያ በአንድ ጀምበር 50 ሚሊየን ብር ለመሰብሰብ በተካሄደው ንቅናቄ ለተሳተፉ ሁሉ ምስጋና አቅርበዋል፡፡

ጠ/ሚ ዐቢይ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገፃቸው ÷የዛሬ ጀምበር ወጥታ እስክትጠልቅ ለ #ጽዱኢትዮጵያ ስራችን 50 ሚሊየን ብር ኢትዮጵያውያን ሁሉ ልናዋጣ አቅደን ነበር ብለዋል።

ያሰብነውን ሳናሳካ ጀምበር የሚጠልቅብን አይደለንምና በአንድ ጀምበር ከ154 ሚሊየን ብር በላይ ማዋጣት ችለናል ነው ያሉት።

ኢትዮጵያን ሲያኮሩ የኖሩ አትሌቶች፣ ስፖርተኞች እና ደጋፊዎች፣ የዘወትር አገልጋይ የታክሲ አሽከርካሪዎች፣ ለኅሊናም ለአካባቢም ንፅህና የሚቀኙ ከያንያን፣ ምሁራን፣ ባለሃብቶች በቴሌቶኑ ስፍራ በመገኘት ላደረጉት አስተዋጽዎም ምስጋና አቅርበዋል፡፡

በመላው አለም ሆነው በዛሬዋ ጀምበር በዲጂታል ቴሌቶኑ የተሳተፉ ከ40 ሺህ በላይ ዜጎች ለፅዱ ኢትዮጵያ ያላቸው ምኞት መግለጫ የሆነው አስተዋፅዖ በተግባር በየአካባቢው በሚገነቡ የሕዝብ መፀዳጃዎች ይታወሳል ነው ያሉት።

ይህ ትውልድ ጀምበር ወጥታ በገባች ቁጥር ለመጪው ትውልድ መስፈንጠሪያ የሚሆን ብሩህ እና ፅኑ መሰረት ደልድሎ ያወርሳል ሲሉም በፅሁፋቸው አስፍረዋል።

ምኞት ተግባራችን ሁሉ የተሻለች ኢትዮጵያን በኅብረት ገንብቶ ማቆየት ነው ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ።

FBC