October 5, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

የመራጮች ምዝገባ ተራዘመ

የመራጮች ምዝገባ እስከ ግንቦት 12 ቀን 2016 ዓ.ም ድረስ መራዘሙን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አስታወቀ፡፡በ6ኛው ዙር ጠቅላላ ምርጫ ቀሪ ምርጫ በሚደረግባቸው የቤኒሻንጉል ጉሙዝ እና አፋር ክልሎች እንዲሁም ድጋሚ ምርጫ በሚደረግባቸው በጅግጅጋ 2 እና መስቃንና ማረቆ ምርጫ ክልሎች ሰኔ 9 ቀን 2016 ዓ.ም. ምርጫ ለማከናወን ዝግጅቶች እየተደረገ መሆኑ ይታወቃል፡፡ለዚህም ከሚያዝያ 21 እስከ ግንቦት 5 ቀን 2016 ዓ.ም. የጊዜ ሰሌዳ ወጥቶ የመራጮች ምዝገባ እየተካሄደ እንደሚገኝ ነው ቦርዱ የገለጸው፡፡ነገር ግን የመራጮች ምዝገባ በወጣበት የጊዜ ሰሌዳ ወቅት ተደራራቢ የሕዝብና የሃይማኖት በዓላት ስለነበሩ፣ የመራጮች ምዝገባ የሚደረግባቸው አንዳንድ ምርጫ ጣቢያዎች በወቅቱ ባለመከፈታቸው ብሎም በምርጫ የሚወዳደሩት የፓለቲካ ፓርቲዎችም በተመሳሳይ ሁኔታ የመራጮች ምዝገባ ቀን እንዲራዘም በመጠየቃቸው የመራጮችን የምዝገባ ቀን እስከ ግንቦት 12 ቀን 2016 ዓ.ም. ማራዘሙን ቦርዱ አስታውቋል፡፡በመሆኑም ምርጫ በሚካሄድባቸው ምርጫ ክልሎች የሚገኙ መራጮች የተሰጠውን የመራጮች የምዝገባ ወቅት በመጠቀም ለምዝገባ ብቁ የሚያደርጉ ማስረጃዎችን በመያዝ በየአካባቢያቸው በሚገኙ ምርጫ ጣቢያዎች በመገኘት በመራጭነት መመዝገብ እንደሚችሉ ተመላክቷል፡፡

EBC