July 2, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

ቻይና ከጨረቃ የሩቅ ክፍል ናሙና ለማምጣት የጠፈር መንኮራኩር አመጠቀች

ቸንጅ-6 ፕሮብ ከሮኬቷ ከተለያየች በኋላ ወደ ጨረቃ ኦርቢት ለመድረስ ከአራት እስከ አምስት ቀናት እንደሚፈጅባት ይጠበቃል

መንኮራኩሯ ሁለት ኪሎሜትር በሚሸፍን ቦታ የድንጋይ እና አፈር ናሙና ቁፋሮ እንደምታካሄድ ተገልጿል

ቻይና ከጨረቃ የሩቅ ክፍል የድንጋይ እና የአፈር ናሙና ለማምጣት ለሁለት ወር የምትቆይ ሰው አልባ የጠፈር መንኮራኩር በዛሬው እለት አምጥቃለች።

ቻይና እንዲህ አይነት ሙከራ በማድረግ የመጀመሪያዋ ሀገር ሆናለች ተብሏል።

ዘ ሎንግ ማርች-5 የተባለችው የቻይና ሮኬት ስምንት ሜትሪክ ቶን ክብደት ያላትን ቸንጅ-6 ፕሮብ የተባለችውን የጠፈር መንኮራኩር በሀይኒያን ደሴት ከሚገኘው ዌንቻንግ ስፔስ ላውንች ሴንተር ይዛ ተወንጭፋለች።

ቸንጅ-6 በጨረቃ የሩቅ ክፍል በሚገኘው ሳውዝ ፖል አትኪን በማረፍ ናሙና እንድትሰበስብ ተልእኮ ተሰጥቷታል። የዚህች መንኮራኩር መምጠቅ በቻይና የሉናር እና የጠፈር አሰሳ ፕሮግራም ትልቅ እምርታ ተደርጎም ተወስዷል።

“ቻይና እንዲህ አይነት ትልቅ እና ስኬታማ ፕሮግራም በአጭር ጊዜ ማበልጸጓ ትንሽ ሚስጥር ሆኖብናል” ሲሉ በአንደኛው የቸንጂ-6 ሳይንሳዊ ተልእኮ ውስጥ የሚሰሩቲ ፈረንሳያዊው ተመራማሪ ፔሪ ይቬስ መስሊን ተናግረዋል።

በ2018 ቻይና ለመጀመሪያ ጊዜ ሩቅ በተባለው የጨረቃ ክፍል ቸንጅ-4 የተሰኘች ሰው አልባ መንኮራኩር ማሳረፍ ችላለች። 

በ2020 ቸንጅ-5 መንኮራኩር የሰው ልጆች በ44 አመት ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ናሙና እንዲያመጡ ያስቻለች ሲሆን ቸንጅ-6 ደግሞ ድብቅ ከሆነው የጨረቃ ክፍል ናሙና በማማጣት ቻይናን የመጀመሪያ ሀገር ልታደርጋት ትችላለች ተብሏል።

ከፈረንሳይ፣ ከጣሊያን፣ ከፓኪስታን፣ አውሮፓ ስፔስ ኤጀንሲ የመጡ ሳይንቲስቶች፣ ዲፕሎማቶች እና የስፔስ ኤጀንሲ ባለስልጣናት የቸንጅ-6 መንኮራኩርን የማምጠቅ ሂደት በአካል ተገኝተው ተመልክተዋል።  ነገርግን የቻይና ናሽናል ስፔስ አድሚኒስትሬሽን(ሲኤንኤስኤ) የሉናር ኤክስፕሎሬሽን እና ስፔስ ፕሮግራም ምክትል ዳይሬክተር ጄ ፒንግ እንዳሉት ከሆነ ሁነቱን ለማየት ያመለከተ የአሜሪካ ኩባንያ የለም።

ቻይና ከአሜሪካው የስፔስ ኤጀንሲ ናሳ ጋር እንዳትተባበር በአሜሪካ ህግ ክልከላ ተጥሎባታል።

ቸንጅ-6 ፕሮብ ከሮኬቷ ከተለያየች በኋላ ወደ ጨረቃ ኦርቢት ለመድረስ ከአራት እስከ አምስት ቀናት እንደሚፈጅባት ይጠበቃል። ከጥቂት ሳምንታት በኋላ በሰኔ ወር ወደ መሬት ትመለሳለች።

መንኮራኩሯ በኢነር ሞንጎሊያ ከማረፏ በፊት ሁለት ኪሎሜትር በሚሸፍን ቦታ የናሙና ቁፋሮ እንደምታካሄድም ተገልጿል።

Al-Ain