July 4, 2024

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

የደ/ም/ኢ ህዝቦች ክልል መንግስት የዘንድሮን የፋስካ በዓል ምክንያት በማድረግ ለ926 ታራሚዎች ይቅርታ ማድረጉ ተገለጸ፡፡

የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል መንግስት የዘንድሮን የፋስካ በዓል ምክንያት በማድረግ ለ926 ታራሚዎች ይቅርታ ማድረጉ ተገለጸ፡፡

የክልሉ ማረሚያ ኮሚሽን በአዋጅ ቁጥር 21/2015 በተሰጠዉ ስልጣን መሰረት በፍርድ ቤቶች ዉሳኔ የሚላኩ የህግ ታራሚዎችን በስሩ ባሉ ስድስቱም ማረሚያ ቤቶች ተቀብሎ ደህንነታቸዉን በመጠበቅና መሰረታዊ ፍላጎታቸዉን በማሟላት በሚሰጠዉ ዘመናዊ ትምህርትና የክህሎት ስልጠና አገልግሎት የአስተሳሰብና የስነ ምግባር ለዉጥ አምጥተዉ አምራችና ህግ አክባሪ ዜጋ ሆነዉ እንዲወጡ እየሰራ መሆኑን የክልሉ ፍትህ ቢሮ ኃላፊ አቶ እሸቱ ጎዴቶ ተናግረዋል ።

በዚሁ መሠረት በክልሉ ባሉ ማረሚያ ቤቶች ሲታረሙና ሲታነጹ ከቆዩ ታራሚዎች የይቅርታ ጥያቄ ካቀረቡት ወስጥ የይቅርታ አዋጅ፣ደንብና መመሪያ መሰረት መስፈርቱን የሚያሟሉ ታራሚዎችን ማመልከቻ የይቅርታ ቦርዱ ሲመረምር ከመንግስት ከህዝብና ከታራሚ ጥቅም አንፃር በማገንዘብ ነዉ ብለዋል፡፡

በተደረገዉ ምርመራም አጠቃላይ የይቅርታ ጥያቄ ያቀረቡት ወንድ 955 ሴት 23 በድምሩ 978 ሲሆኑ ከነዚህም የይቀርታ ጥያቄ ተቀባይነት ያገኙ ወንድ 903 ሴት 23 ድምር 926 መሆናቸው ታውቋል።

ከነዚህ ዉስጥ 920 ታራሚዎች ከእስር የሚለቀቁ ሲሆን 6ቱ ታራሚዎች የእረስራት ቅናሽ የተደረገላቸዉ እንደሆነ ነው የተገለጸው፡፡

ቀሪዎቹ 52 ታራሚዎች የይቅርታ ጥያቄያቸዉ ህጉ የሚጠይቀዉን መስፈርት ባለማሟላቱ ዉድቅ የተደረገባቸዉ ናቸዉ፡፡

በማረሚያ ቤት ቆይታ ጊዚያቸዉ ከፍርዳቸዉ አንድ ሁለተኛ እና አንድ ሶስተኛ የሚያሟሉና በማረሚያ ተቋሙ በነበራቸዉ ቆይታ ስለመታረማቸዉ ፤ ስለመታነጻቸዉና ስለመልካም ባህሪያቸዉ በየደረጃዉ ከሚገኙ የፀጥታ ተቋማት በቂ ማረጋገጫ የተሰጣቸዉ ታራሚዎች የይቅርታ ተጠቃሚ መሆናቸዉንም ተናግረዋል ፡፡

በመጨረሻም ይቅርታ ጥያቄያቸዉ ተቀባይነት አገኝቶ ከእስር የሚለቀቁ ታራሚዎች ለወደፊቱ ለህብረተሰቡ የወንጀል ስጋት ሳይሆኑ የሠላም ሰባኪ፤ አምራችና ህግ አክባሪ ዜጋ ሆነዉ ህብረተሰቡን እንድቀላቀሉና ህብረተሰቡም በበጎ እንድቀበላቸዉ አስገንዝበል።

ቸርነት አባተ